Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ለሁለንተናዊ ጥቅማችን

0 320

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

ለሁለንተናዊ ጥቅማችን

                                                            ሶሪ ገመዳ

መንግሥት በአገራችን ውስጥ የሕዝቡን የኑሮ ውድነት ለማባባስ የሚችሉ ህገ ወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠር ጥረት በማድረግ ውጤቶችንም እያስመዘገበ ነው። ጥረቶቹ ኢንቨስትመንትን የሚያስፋፉና በቀጣይም ሰላማችንን እስካረጋገጥን ድረስ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂነት ያላቸው ግዙፍ ኩባንያዎች ወደ እኛ በመምጣት በጋራ ስራ እንዲሰሩ የሚያደርጉ ናቸው።

እርግጥ ሰላማችን አስተማማኝ ከሆነ፣ እንደ የገጠር ኢንዱስትሪ ልማት ፖርክን የመሳሰሉ የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች ይስፋፋሉ። የኦሮሚያ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ፓርክ የደረሰበትን አፈጻጸም ሂደት እና በሌሎች ክልሎች የተጀመሩ የግብርና ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች የአገራችንን ኢኮኖሚ ከግብርና ወደ ኢንዱሰትሪ በማሸጋገር፣ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት፣ የሥራ እድልን በመፍጠር እና እሴት በመጨመር ሁለንተናዊ ጥቅማችንን የሚያረጋግጡ ናቸው። ስለሆነም ሁለንተናዊ ጥቅማችንን ለማስጠበቅ ሰላምን እንደ ዓይን ብሌን መንከባከብ ያስፈልጋል።

የኢንዱስትሪ ልማት ፓርክ ኢኮኖሚውን ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ሊያሸጋግሩ የሚችሉ ናቸው። በሌላ አገላለጽ መዋቅራዊ ለውጥ ያመጣሉ ማለት ነው። ይህ ሁኔታ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ (ኤክስፖርት በማድረግ) ሊገለጽም ይችላል።

የኢኮኖሚ ሽግግሩን ገቢራዊ በማድረግ ረገድ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪው የኤክስፖርት ሚናው ሁነኛ ማሳያ ነው። ዛሬን ከነገ ጋር ብናስተያየው የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ አሁን ካለው ሁኔታ አኳያ ሲታይ ከጠቅላላው የኤክስፖርት ገቢ ከአስር በመቶ አይበልጥም።

ያገኘሁት የእቅዱ ሰነድ እንደሚያስረዳው፤ ይህን አሃዝ በ2012 ዓ.ም ላይ ወደ 25 በመቶ ከፍ ለማድረግ ታስቧል። በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ዘርፉ አምስት ቢልዮን ዶላር ገቢ እንዲያስገኝ ለማድረግ ታስቧል። መንግስት ባለፉት አምስት ወራቶች ውስጥ ተገቢውን ድጋፍ እያደረገ ነው።

ወደፊት በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የሚኖረው የሰው ኃይል አሰላለፍና የስራ ፈጠራ የመዋቅራዊ ሽግግሩ የማዕዘን ድንጋይ መሆኑ አይቀርም። አሁን ባለው አሃዝ መሰረት በመካከለኛና በከፍተኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች ውስጥ የተሰማራው የሰው ኃይል ከሶስት መቶ ሃምሳ ሺህ በላይ ይገመታል።

ከላይ የተመለከተው ቁጥር በሁለተኛው የልማት ዕቅድ እና ከእርሱም ቀጥሎ ባሉት አምስት ዓመታት በአራት እጥፍ እንደሚያድግ መረጃዎች ይጠቁማሉ። አሃዙ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ዜጎች በዘርፉ እንዲሰማሩ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን ያሳያል።

አሁን የምንገኝበት ሁለተኛው የልማት ዕቅድ ድርሻ የተያዘውን የአስር ዓመት ዕቅድ በግማሽ እንዲሳካ ማድረግ ነው። ይህም ወደ ሰባት መቶ ሃምሳ ሺህ የሚጠጉ ዜጎች በዘርፉ እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠርን ያካትታል። ይህ ዕውን ከሆነም አሁን ያለውን የሰው ኃይል ስራ ፈጠራን የሚፈጥር ነው።

እቅዱን ለማሳካት ርብርብ ማድረግ ያስፈልጋል። ዘርፉ በተለይ ወጣቶችንና ሴቶችን የሚያሳትፍና በላቀ ደረጃ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ የዕቅዱን ተግባራዊነት አቅም በፈቀደ መጠን ማረጋገጥ ይገባል።

መንግሥት ለጥቃቅንና አነስተኛና መካከለኛ እንዲሁም ለከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች የተሰጠው ትኩረት የመዋቅራዊ ሽግግሩን የሚያሳልጥ ነው። ኤክስፖርት መር የኢንዱስትሪ አቅጣጫን ለመከተልና ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን ለመቀነስ እየተደረገ ያለው ጥረት ወሳኝ ነው።  

እርግጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መሰረቱ ይህን ያህል የሚያስመካ አይደለም። ይሁን እንጂ በአሁኑ ሰዓት እየተከናወኑ ያሉት ተግባሮች መሰረቱን እያሰፉት ነው። ይሁንና አሁንም ቢሆን ሀገራችን በዘርፉ ለውጥ እንድታመጣ በዋነኛነት ኢንቨስትመንትን ማስፋፋትና ማጎልበት አለባት።

በዚህ ረገድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የውጭ ባለሃብቶች በገጠር ኢንዱስትሪዎች በቀጥታ እንዲሳተፉ እየተጫወቱ ያሉት ሚና ጉልህ ነው። በጥቂት ወራቶች ውስጥ በርካታ ስራዎችን መስራታቸው ሊያስመሰግናቸው ይገባል።

በአሁኑ ሰዓት የውጭ ባለሃብቶች በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ ተሳትፈው እያሳዩት ያለው ለውጥ አበረታች ነው። በዶክተር አብይ አማካኝነት ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ብርቱ ጥረት እየተደረገ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፍተኛ አቅምና ፍላጎት እንዲሁም በአፈፃፀማቸው ጥሩ ስምና ዝና ያላቸውን የውጭ ኩባንያዎች በመመልመልና የማግባባት ስራ በማከናወን የዘርፉን ዕድገት እንዲያሳድጉ የማግባባት ስራ እየሰሩ ነው።

ባለሃብቶቹን ኤክስፖርት ተኮር በሆኑ የማኑፋክቸሪንግ ውጤቶች ላይ በማሰማራት አገራችን ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ ለማድረግ እያከናወኑ ያሉት ስራ አክብሮትን የሚያጎናጽፋቸው ነው ብዬ አምናለሁ።

እርግጥ ኢትዮጵያ የውጭ ባለሃብቶች ኤክስፖርት ተኮር በሆኑ ዘርፎች ውስጥ እንዲካተቱ ስታደርግ፤ ለአገር ውስጥ ባለሃብቶች ቦታ ሰጥታ ነው። አቅም ያላቸው የአገር ውስጥ ባለሃብቶች መዋዕለ ንዋያቸውን በዘርፉ እንዲያፈሱ ጥረት እየተደረገ ነው።

በቂ ድጋፍና ማበረታቻ እየተሰጣቸው በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪው ዘርፍ ገቢ ምርቶችን በሚተኩ ዘርፎች ጭምር እንዲሳተፉ እየተደረገ ነው። ስራቸው ለሌሎች ሀገር በቀል ባለሃብቶች አርአያ እንዲሆንና ባለሃብቶቹም ተስበው ወደ ተመሳሳይ አገራዊ ስራ እንዲገቡ እንዲበረታቱ የሚያደርግ ነው።

አገራችን ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ለመሸጋገር የምታደርጋቸው ጥረቶች የህዝቦችን ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ናቸው። በተለይም የገጠር ኢንዱስትሪዎች በዚህ ረገፍ ጉልህ ሚና አላቸው።

ኢንዱስትሪዎቹ ስራን በመፍጠር የዜጎችን ገቢ ያሳድጋሉ። የዜጎች ገቢ ሲያድግም አገራችን እንደ አገር ወደ ነበረችበት ገናናነት እንድትመለስ ያደርጋታል። ይህ እንዲሆንና ሁለንተናዊ ጥቅማችን እንዲጠበቅ የህዝቦች ሰላምና ጸጥታ በአስተማማኝ ሁኔታ መረጋገጥ ይኖርበታል።

 

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy