CURRENT

በሃገር ውስጥ እና በውጭ ያላችሁ ውድ ኢትዮጵያውያን!

አዲስ አመት የአዲስ ምዕራፍ መክፈቻ ነው ኢትዮጵያችን ታላቅ አገር ናት የታላቅ ህዝብ አገርም ናት

By Admin

September 09, 2018

በሃገር ውስጥ እና በውጭ ያላችሁ ውድ ኢትዮጵያውያን!

በሃገራችን የቀን አቆጣጠር ቀመር መሰረት አሮጌውን የ~2010 ዓመት በክብር ለመሸኘት፤ እንዲሁም የ~2011 አዲስ ዓመትን ደግሞ በፍቅር ለመቀበል . . . በታላቅ ዝግጅት ላይ እንገኛለን። እነሆ! የምናጠናቅቀው የ~2010 ዓመት በሃገራችን ታሪክ ዑደት ውስጥ ልዩ ስፍራ የሚይዝ ነው። በህዝባችን ብርቱ ትግል የለውጥ ድባብ ዳር እስከ ዳር የነገሰበት እንዲሁም ቀድመው የተፈፀሙ በደሎችን እና ጥፋቶችን በይቅርታ ለመሻገር ልባዊ መነሳሳት የናኘበት ድንቅ ዓመት ነበር። በ~2010 ዓመት. . . በእያንዳንዱ ዜጋችን ነፍስያ ውስጥ የሚንቀለቀለው የለውጥ ሞገድ እና ልባዊ የይቅርታ መነሳሳት እንደ ማለዳ ጤዛ ታይቶ የሚጠፋ ሳይሆን በትውልዱ ባለቤትነት እየጠለቀ፥ እየጠበቀ እና እየደመቀ የሚቀጥል ሲሆን አጠቃላይ የትግሉ ውጤት ለ-2011 አዲሱ ዓመት . . . ለእናት ሃገራችን የተበረከተ ልዩ “የድል ስጦታ” ተደርጎ የሚወሰድ ነው። ይህ “የድል ስጦታ” በአዲሱ የ~2011 ዓመት በቀጣይ ሌሎች ተደማሪ ድሎችን የምንጎናፀፍበት መስፈንጠሪያ ዕድል በመሆኑ በዕምነት ልንጠብቀው ይገባል። የተቀጣጠለው የለውጥ ስሜት ቀጣይነቱን በማረጋገጥ አስቀድመው የተጀመሩ በጎ ስራዎችን እያስፋፋን፤ የጎደለውን እየሞላን፤ የቀደመውን ደግሞ በእጅጉ እያላቅን ድሃው ደጅ ዘልቆ የሚደርስ ተጨባጭ ስራ መስራት ይጠበቅብናል፡፡ በአንፃሩ በኛ ዘመን የተፈፀሙ ጥፋቶች እና በደሎች ዳግም እንዳይፈፀሙ ብቻ ሳይሆን በአስተሳሰብ ደረጃ በትውልዱ ልቦና ውስጥ ታትመው እንዳይዘልቁ በእውነተኛ ይቅርታ ልንሽራቸው እና ልንሻገራቸው ይገባል። በቂም እና በቁርሾ ስሜት ውስጥ መዳከር ሽራፊ ፀጋ እንደሌለው ለረጅም ዓመታት ካለፍንበት የጥፋት ጎዳና እና ታሪክ ከማያልፈው የክፋት ዳና በሚገባ አይተነዋል፡፡ እርግጥ ነው! ባልነበርንበት ዘመናት ለተፈፀሙ ጥፋቶች በምንም መልኩ ልናርማቸው አንችልም፤ ነገር ግን ልንማርባቸው እንችላለን፡፡ ከእንግዲህ በኋላ . . . ታሪክ የምንማርበት እንጂ የምንተራሰው ሊሆን አይገባም፡፡ እነሆ ዛሬ! . . . ካለፍንበት እኩይ ታሪክ ከልብ ልንማርበት እና ከእውነት ልንለወጥበት የሚገባን ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ለዚህም ነው! . . . አሮጌው ዘመን አልፎ አዲሱ ዘመን ሲተካ በታላቅ ብሄራዊ ስሜት “በፍቅር እንደመር ~ በይቅርታ እንሻገር!” ያልነው፡፡ በይቅርታ እርቅን ፤ በፍቅር ደግሞ ሰላምን የምንገበይትበት ዘመን ልንፈጥር ግድ ይላል፡፡ ለሃገራችን የዕድገት ትንሳኤ በእጃችን የጨበጥነውን ወርቃማ ዕድል ከፊት ለፊት በርካታ ወርቃማ ድል ለማስመዝገብ የሚያስችለን በመሆኑ በጥበብ ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ መጪው ዘመን ሁላችንም በተሰማራንበት ዘርፍ የምንናገረውን በተግባር ሆነን የምንገኝበት፤ በንፁህ ልብ የምንተሳሰብበት፤ እንዲሁም አንድነታችን የሚጠብቅበት እንዲሆን ከልብ እመኛለሁ! መልካም አዲስ ዓመት!