CURRENT

መንግስት በሃገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ያጋጠሙ ግጭቶችን ሊያስቆም ይገባል…የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን

By Admin

October 04, 2018

 በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሼ ዞንና በደቡብ ክልል ካፋና ሸካ ዞኖች ያጋጠመውን የዜጎች መፈናቀል መንግስት በፍጥነት ሊያስቆመው እንደሚገባ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን አስታወቀ።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር አዲሱ ገብረእግዚአብሄር ለጋዘጠኞች በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሽ ዞን አምስት ወረዳዎች አሳሳቢ ሁኔታዎች ተፈጥረዋል፡፡

በተመሳሳይ በካፋና ሸካ ዞኖች በተፈጠረ ግጭትና ሁከት በርካታ ዜጎች መፈናቀላቸውን ገልጸዋል፡፡

“በአካባቢዎች አለመረጋጋት ምክንያት የዜጎች በነጻነት የመዘዋወር፣ንብረት የማፍራትና ሌሎች ህገ መንግስታዊ መብቶች እየተሸረሸሩ በመሆናቸው መንግስት በፍጥነት ሊያስቆመው ይገባል” ብለዋል።

ግጭቶቹ በተከሰቱባቸው አካባቢዎች እያጋጠመ ያለውን የዜጎች መፈናቀል ለመርመር ባለሙያዎች ቢላኩም ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው ምርመራው አለመጀመሩን ጠቅሰው ከነገ ጀምሮ ወደ ስራ እንዲገቡ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

በካማሼ ዞን አምስት ወረዳዎች ጉዳዩ አሳሳቢ በመሆኑ በተወሰኑ ወረዳዎች የመከላከያ ሃይል ገብቶ እያረጋጋ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

የዜጎች በነጻነት የመዘዋወር፣ ንብረት የማፍራትና የመስራት መብት አሳሳቢ ሁኔታ እየገጠመው በመሆኑ በክልልም በፌደራልም ያሉ የጸጥታ አካላት ሃላፊነታቸውን በተገቢው ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

“የዜጎች መብት እየተረገጠ ባለበት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት መገንባት አይቻልም” ያሉት ዶክተር አዲሱ ችግሩ እንዳይባባስ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ ጠይቀዋል፡፡

“በአካባቢዎቹ ያሉ ዜጎች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች በጥናት መመለስና የህግ የበላይነትንና ተጠያቂነትን በማስፈን መብታቸውን ማስከበር ይገባል” ብለዋል፡፡

ከአደጋ መካላከልና ከፀጥታ አካላት ጋር በሚያከናውኑት ተግባር የህግ የበላይነት እንዲከበርና ሰብዓዊ እርዳታ እንዲያገኙ እየሰሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡

የጸጥታና የመንግስት አካላት በተገቢው የመካከል ስራ ባለመከናቸው ችግሩ መባባሱን የተናገሩት ሃላፊው “መንግስት የግጭት ምልክቶችን  አስቀድሞ የማጥናት ስልት ሊከተል ይገባል” ብለዋል።

ዘላቂ ሰላም ለማስፈን አሁን እያጋጠመ ያለውን ግጭቱን በተለመደው መልክ መፍታት እንደማቻል ተናግረዋል።

ኮሚሽኑ ባለፉት ሶስት አመታት በነበረው ሁከትና ግጭት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ከቄያቸው መፈናቀላቸውንና ያፈሩትን ንብረት ማጣታቸውን በምርመራ ማረጋገጡን አስታውሰዋል፡፡

ውጤቱን ለሚመለከተው አካል ይፋ በማድረግ ተጠያቂ ያደረጋቸው አካላት መኖራቸውንም ተናግረዋል፡፡