NEWS

የአማራ ክልል ሕዝብ ሰላምን ለማስፈንና ለውጡን ለማራመድ ድርሻውን እንዲወጣ ርዕሰ መስተዳድሩ ጠየቁ

By Admin

March 25, 2019

 የአማራ ክልል ሕዝብ ሰላምን ለማስፈንና ለውጡን ለማራመድ ከአመራሩ ጎን በመቆም ድርሻውን መወጣት እንደሚጠበቅበት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጠየቁ።

”በአማራ ክልል የታክስ  አምባሳደሮች የምክክር መድረክ” ትናንት ተካሂዷል።

ርዕሰ መስተዳድሩ ዶክተር አምባቸው መኮንን በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት የክልሉ ሕዝብ እስከ ሕይወት መስዋትነት ዋጋ የከፈለበት ለውጥ  ስኬታማ እንዲሆን መሥራት አለበት።

”ሕዝቡ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንድሆን ባሳየው ፍላጎት ምክንያት የሕዝቡን አደራ ተሸክሜያለሁ” ያሉት ዶክተር አምባቸው፣ ክልሉን አስተማማኝ የሰላም ቀጠና ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ሕዝቡ በኢትዮጵያዊነት አስተሳሰብ  መስራት ይጠበቅበታል ብለዋል።

ሕዝቡ ከክልል እስከ ወረዳ ድረስ ካሉ አመራሮች ጋር በመቀናጅት ለውጡን ለማስቀጠል እንዲተጋም ጠይቀዋል።

ለውጡ እንደ ክልልም ሆነ እንደ አገር መሠረት እንደይኖረው በተናጠል ሳይሆን፡ በጋራ መቆም እንደሚያስፈልግ ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል።

የሕዝቡን ፍላጎት የማይገነዘብ በየትኛውም ደረጃ ላይ የሚገኝ አመራር ደግሞ በተጨባጭ ማስረጃ ከተደረሰበት የሕዝቡን ስነ-ልቡና በሚረዳ አመራር ይተካል ብለዋል።

የክልሉን ሰላምና ልማት በማይናጋ መሠረት ለማስቀመጥ የሕግ የበላይነት መረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን  ዶክተር አምባቸው አመልክተዋል።

የክልሉ መንግሥት አዲሱ አመራር የመጀመሪያው ሥራ ሰላምን ማስከበር እንደሆነ ያስረዱት ርዕሰ መስተዳድሩ፣በሰላማዊ መንገድ ወደ ክልሉ የገቡ ታጥቀው የነበሩ ኃይሎች እንቅስቃሴ ከክልሉ የጸጥታ መዋቅር ጋር ከመቀናጀት ውጭ አማራጭ እንደሌላቸው አስታውቀዋል።

”ለውጡ የድሃ አገር ለውጥ ባይሆን ኖሮ ፤ የዓለም መገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ይሆን ነበር” ብለዋል።

”በለሆሳስ እያሳሳቀ የመጣ ለውጥ በዓለም ላይም የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም” ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ለውጡ የኢትዮጵያውያንን የስልጣኔ ደረጃ እንዳሳየ አመልክተዋል።

”መላ ኢትዮጵያውያንን አንድ ያደረገ የዴሞክራሲ ምልክት የሆነን ለወጥ  ለመቀልበስ የሚሞክር ኃይል ስላለ እሱን ለመከላከል ሕዝቡ ከለውጡ አመራር ጎን መሰለፍ ይጠበቅበታል” በማለትም ተናግረዋል።

የሰሜን ሸዋ ዞን የታክስ አምባሳደር አቶ ወንድም ይሁኔ በበኩላቸው ሕዝቡ ከለውጥ አመራሩ ጎን እንዲቆም  ለመደገፍ ሕዝቡን  እንደሚያስተባበሩ ገልጸዋል።

”ዶክተር አምባቸው ሕዝቡ ከጎናቸው እንዲሰለፍ ያስተላለፉትን መልዕክት እውን አንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም” ያሉት ደግሞ የምስራቅ ጎጃም ዞን የታክስ  አምባሳደር አቶ ቆምጬ አምባው ናቸው።

ዶክተር አምባቸውና ካቢኔያቸው በየደረጃው ያለውን የለውጥ አደናቃፊ አመራር ላይ ሕጋዊ እርምጃ  እንዲወስዱም ጠይቀዋል።

ዶክተር አምባቸው መኮንን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው የተመረጡት ባለፈው ወር መጨረሻ ነበር።